የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ አስተዳደራዊ ፍርድ ቤት ከ2019 እስከ 2023 ዓ.ም የሚተገብረውን የአምስት ዓመት ረቂቅ ስትራቴጂክ እቅድ ከሰራተኞቹ ጋር ውይይት አካሄደ።
ስትራቴጂክ እቅዱ በካፒታል ገበያ አዋጅ ቁጥር 1248/2013 ለፍርድ ቤቱ የተሰጡ ስልጣንና ኃላፊነቶችን መሰረት በማድረግ ከመንግስት ፖሊሲና አቅጣጫ ጋር በተጣጣመ መልኩ የተዘጋጀ ሲሆን፣ ሶስት ዋና ዋና የትኩረት መስኮችን ያካትታል።
እነዚህም ተቋማዊ የመፈጸም፣ የማስፈጸምና የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትን ማሳደግ፣ ጥራት ያለውና ቀልጣፋ ውሳኔ በመስጠት የካፒታል ገበያውን ተዓማኒነት ማጠናከር እንዲሁም የካፒታል ገበያ የህግ ማዕቀፍ ስርጸት እና አጋርነትን ማጠናከር ናቸው።
በውይይቱ ከሰራተኞች በእቅዱ ውስጥ በተካተቱ ግቦች፣ ስትራቴጂዎችና ተግባራት ላይ ግብዓት የተገኘ ሲሆን በቀጣይ የአስተዳደራዊ ፍርድ ቤቱ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የውይይት መድረክ በማካሄድ ተጨማሪ ግብዓቶችን ለማካተት በዝግጅት ላይ ይገኛል።

