የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ አስተዳደራዊ ፍርድ ቤት እና የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በጋራ ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ::
በስምምነቱ መሰረት በካፒታል ገበያ የህግ ማዕቀፍ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ አስተዳደራዊ ፍርድ ቤት በቤንሻንጉል ክልል ለሚገኙ የዳኝነት እና የፍትህ አካላት የተለያዩ ድጋፎችን ለማድረግ የሚያስችል ሲሆን፣ በሁለቱ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብር በማጠናከር ለሀገራችን አዲስ በሆነው የካፒታል ገበያ የሕግ ማዕቀፍ እውቀትና ክህሎት በማሳደግ በዘርፉ ውስብስብ የሆኑ የፋይናንስ እና የኢንቨስትመንት የህግ ጉዳዮችን በመረዳት ፈጣንና ተገማች ፍትህ እንዲሰጡ ለማስቻል ይህ ስምምነት ትልቅ ሚና ይጫወታል ።
ይህም ሰፊ የተፈጥሮ ሀብትና የኢንቨስትመንት አማራጭ ባላት የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጠንካራ የካፒታል ገበያ የህግ ስርዓት መዘርጋቱ፣ ወደ ክልሉ ለሚመጡ ኩባንያዎች በህግ አግባብ እንዲሰሩ በማድረግ ለኢንቨስተሮችን ዋስትና በመስጠት የካፒታል ገበያ ተዓማኒነት በእጅጉ እንደሚያሳድገው ተጠቁሟል።
ይህ ስምምነት በሁለቱ ተቋማት መካከል ዘላቂነት ያለው ትብብር በመፍጠር በሀገር አቀፍ ደረጃ ወጥ የሆነ የካፒታል ገበያ የህግ አተረጓጎም ስርዓትን ለመፍጠር የሚያስችል ስትራቴጂካዊ አጋርነት ነው። እርምጃው የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዘመናዊውን የፋይናንስ ስርአት ለማስተናገድ ራሱን እያዘጋጀ መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን ለሌሎች ክልሎችም በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ ነው፡፡



