የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ አስተዳደራዊ ፍርድቤት ከኦሮሚያ ክልል ለተገኙ የተለያዩ ተቋማት ስለ ካፒታል ገበያ ጽንሰ ሀሳብ እና አጠቃላይ የካፒታል ገበያ የህግ ማዕቀፎች በተመለከተ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ እያካሄደ ነው።
አስተዳደራዊ ፍርድቤቱ በአዳማ ከተማ እያካሄደ በሚገኘው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድቤት ዳኞች፣ የኦሮሚያ ክልል ፍትህ ቢሮ አቃቢያነ ህግ፣ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን መኮንኖች፣ የኦሮሚያ የስነ-ምግባርና ፀረሙስና ኮሚሽን ባለሙያዎች እንዲሁም የኦሮሚያ ፕሬዘዳንት ፅ/ቤት ከፍተኛ ኃላፊዎች በአጠቃላይ ከ50 በላይ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል።
በግንዛቤ ማስጨበጫ መርሀግብሩ ወቅት የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የአስተዳደር ፍርድቤቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ አብነት ዘርፉ መድረኩ ስለካፒታል ገበያ መሰረታዊ ግንዛቤ ከማስጨበጡም በላይ አስተዳደር ፍርድቤቱ በስልጠናው ከተገኙ ተቋማት ጋር ወደፊት በጋራ ስለሚሰራ የትውውቅ መድረክም ጭምር ነው ብለዋል።
በጠዋቱ ክፍለጊዜ ስለካፒታል ገበያ የህግ ማዕቀፍ የግንዛቤ ማስጨበጫ የሰጡት አቶ በሱፈቃድ ተረፈ በበኩላቸው የካፒታል ገበያ ባለስልጣን፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ፣ የማዕከላዊ የሰነደ ሙዓለ ነዋይ ግምጃ ቤት እና የአስተዳደራዊ ፍርድቤቱን ሚና በተመለከተ በስፋት አብራርተዋል።
የአስተዳደራዊ ፍርድቤቱ ተቋማቱ የሚሰጡት ውሳኔዎች ላይ የሚፈጠሩ ቅሬታዎችን በማረም ረገድ ያለውን አስተዋጽኦ አቶ በሱፈቃድ ግንዛቤ አስጨብጠዋል።
